Friday, August 18, 2017

የአብርሃም በጎች ነን

                                               ዘነበ ታምራት ገብረ ማርያም

ቀን ጠባ ቀን መሸ ለኛ ምን ፋይዳ አለው
መጎተት መታሰር የቀን ውሏችን ነው
መቀጥቀጥ መደብደብ ቁርስ ምሳችን ነው
ካለፍርድ መረሸን የበየኑብን ነው
አቤቱታ ሰሚ ኧረ የት ነው ያለው
የዓለም ማሕበሩ ኒውዮርክ ላይ ያለው
የተመድ የሚሉት ሺባ ድርጅት ነው
የዓለም ፍርድ ቤቱ ዤኔቫ ላይ ያለው
ወይንስ ዋሽንግተን ኸዋይት ሃውስ ነው
አቤት የሚባለው
ለዓለም ፍርድ ቤት አቃቤ ሕግ ነው
ወይንስ ለአምኔስቲ የመብት ተሟጋች ነው
አቤቱታ ሰሚ ተው በቃ የሚለው
ሕዝብን ከአምባ ገነን ቀጥቃጭ የሚያድነው
የትኛው ማሕበር የትኛው ተቋም ነው
አምባ ገነን ከቶ በማን ነው እሚዳኘው
በጴጥሮስ ጋሊ ነው
ወይ በአሜሪካኑ በቢል ክሊንተን ነው
እየተቀጠቀጥን በአምባገነን በትር
ሰለባ እየሆንን ለወያኔ አሩር
የፍርድ ያለህ እያልን የምንጮኽ ዘወትር
ጠፍቶን አኮ አይደለም አፀፋ መሰንዘር
ነገር ግን ታጋዮች እመዐሕድ ውስጥ ያለን
ፍጹም ንጹህ ዜጎች በሰላም የምናምን
ለመስዋእት የቀረብን የአብርሃም በጎች ነን
የምንገደለው በጨለማ በቀን
ደማችን የሚፈስ ለአገር ለወገን
ሺበሺ እያለቅነ ወደኋላ የማንል
አጥተነው አይደለም የጫካውን ትግል
ነገር ግን ነን እኛ መተኪያ የሌለን
የቁርጥ ቀን ልጆች ኸመዐሕድ ያለን
የአገር ፍቅር እሳት የሚያንገበግበን
ትውልደ አማራ ፤ የሰላም አርበኞች ፤ የአብርሃም በጎች ነን
ሆኖም ችለን፤ ችለን፤
እምብየው ካላችሁ መላ እንመታለን፤
ካችአምና ያኘክነውን ዘንድሮ እንውጣለን፤
በገድሎ መጣሉ እንበልጣለን እንጂ መች እኛ እናንሳለን።
በአብሮ መኖር አምነን ዛሬም እንደ ጥንቱ
ነው ብለን ነው እንጂ የሰላም ሰብሃቱ
አቤት የምንለው በየአደባባዩ፤ በየፍርድ ቤቱ
መች ጠፋን ከቶውን ለእኛ ወንድነቱ
ነገር ግን አያልቅም የአማራ ትግስቱ
እኛ በትእግስት መላ እናፈላልግ እናንት ጮቤ ምቱ
ተመድ ነው ዋይት ሃውዝ የሚቀርብ ሙግቱ
ክስ የሚቀርብበት የት ነው ፍርድ ቤቱ
ኸዋይት ሃውዝ ነው ዋና ጽሕፈት ቤቱ
ወይንስ ከስተጀርባው ኸመኖሪያ ቤቱ
ኸፕሬዘዳንቱ?
የትነው መሟገቻው እንዴት ነው ሥርአቱ
የት ነው አቤት የሚል ሕዝብ ሲደፈር መብቱ
ወያኔ ሰው ሲፈጅ ዘር እየቆጠረ በአያቱ በአባቱ።
ዓለም አቀፍ ያሉት የታል ፍርድ ቤቱ
ፍርድ ቤት ከሌለ ካልተሰማ እውነቱ
ጆሮ ዳባ ካለ ተሰምቶ ጩኽቱ
የተመድ ሽምድምድ አቅም የሌለው ነው፤
ጋሊ ድሮውንም ውሃ ውሃ የ የሚል የጥንት ጠላቴ ነው፤
የተመድ በውስጡ ሰው የለውሰው የለው
ዋይት ሃውዝ ድንጋይ ነው
ክሊንተንም ሰምቶ ሰማሁ የማይል ነው
ዋይት ሃውሰ በውስጡ ሰው የለው ሰው የለው
እኔ አቤት አልልም ለቢል ክሊንተን
አልለማመጥም ግብጻዊ ጋሊን
የተመድ ለአገሬ መፍትሄም አይሆን
ያገሬ ልጅ ተነስ እወቀው እቅጩን
አይቼዋለሁኝ የአፍሪካ የፈረንጁን
ያለኸው አንተነህ ትጥክህን አጥብቅ
ለነጻነታችን እንተናነቅ
ያገር ልጅ ቤልጅጌ ያገር ልጅ ምንሽር፤
ያገር ልጅ ጓንዶዬ አንጀቴን የሚያሽር፤
ያገር ልጅ ጠብመንጃ የአገር ልጅ አልቤን፤
ጠፍረህ አምጣልኝ አስረህ እጅ እጁን፤
አቶስታሹንና ቀጥቃጭ ቀጥቃጩን።




                                      









No comments:

Post a Comment